በሶማሊያ የግዛት አንድነት ላይ የኢትዮጵያ መንግስት ምንም አይነት ጥያቄም ይሁን ብዥታ የለውም ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተናገሩ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ዲፕሎማሲን በተመለከተ ለተነሳላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽና ማብራሪያ፤ “የሶማሊያ ህዝብ ጎረቤት ብቻ ሳይሆን ወንድምና እህት ህዝብ ነው፤ ለሶማሊያ ሰላምና አንድነት ሞተናል” ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ ለሶማሊያ ግዛት አንድነት ከየትኛውም ሀገር በላይ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያደረገችና አሁንም ፅኑ እምነት ያለት ሀገር መሆኗን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናገረዋል፡፡
አሁን ያለው መንግስት ለሶማሊያ ያለውን ክብር ከማንኛውም አካል በላይ በተግባር ማሳየቱን ጠቅሰው፤ “ሶማሊያን እንደ ኢትዮጵያ ቆጥረን ሚናችንን ተወጥተናል” ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ ከሶማሌላንድ ጋር ያደረገችው የመግባቢያ ስምምነት አትዮጵያ ለሁሉም ጎረቤቶቿ ላቀረበችው ጥያቄ ምላሽ ስታጣ ምላሽ ከሰጠው አካል ጋር የተደረገ ነው ሲሉም ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ ጥያቄ ወደብ የመጠቀምና መብት የማግኘት ህጋዊ ጥያቄ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ጥያቄው በሰላማዊና በንግግር ምላሽ እንዲያገኝ እየተሰራ ነው፤ ለዚህም ኢትዮጵያ ዝግጁ ናት ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ ከሁሉም ጎረቤት ሀገራት ጋር ለጋር ልማትና ብልፅግና በሰጥቶ መቀበል መርህ ለመስራት ፅኑ ፍላጎት እንዳላትም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያ ከሱዳን፣ ከደቡብ ሱዳን፣ ከሶማሊያ፣ ከኤርትራ፣ ከጅቡቲ እና ከኬንያ ጋር ለጋራ እድገት፣ ልማትና ሰላም በጋራ ለመስራት ቁርጠኛ ናት ሲሉም ተናግረዋል፡፡
የባህር በር ማግኘት ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ፍላጎት ነው ያሉት ጠቅላይ ሚነስትሩ፤ ይህ እውን እንዲሆን ኢትዮጵያ ከሁሉም የጎረቤት ሀገራት ጋር ለጋራ ጥቅም፣ ሰላም እና ብልፅግና ትሰራለች ነው ያሉት፡፡
ኢትዮጵያ የባህር በር የማግኘት መብቷን በሰላማዊና በህጋዊ መንገድ መንገድ በሰጥቶ መቀበል መርህ ለማሳካት ጥረት ማደረጓን ትቀጥላለችም ብለዋል፡፡
EBC


