የድሬዳዋ አስተዳደር ገቢዎች ባለስልጣን በተሻሻለው የፌደራል ገቢ ግብር አዋጅ 1395/2017 ላይ በአስተዳደሩ ለሚገኙ ለንግዱ ማህበረሰብ የግንዛቤ ማስጨበጫ የውይይት መድረክ በዛሬው እለት አካሂዷል።
ውይይቱ በዋናነት የተሻሻለው የገቢ ግብር አዋጅ ቁጥር 1395/2017 ላይ በተለይም የግብር ስርዓቱ ላይ የሚታዩ የፍትሀዊነት ችግሮች ለመቅረፍ የሚያስችሉ የአሰራር ስርዓቶችን በመዘርጋት የወጡ አዋጆችን ለንግዱ ማህበረሰብ ግንዛቤ ለማስጨበጥ አላማ ያደረገ መሆኑ ተገልጿል።
በውይይት መድረኩም የድሬዳዋ አስተዳደር ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ስራአስኪያጅ አቶ አብዱሰላም መሀመድ እንደገለጹት መንግስት ገቢን ለማሳደግ የፋይናንስ እና የታክስ ስርዓቱን ሪፎርም በማድረግ በርካታ ለውጦች እያስመዘገበ መሆኑን ተናግረዋል።
የህዝቡን መሠረታዊ ጥያቄዎች ለመመለስ የታክስ አሰራሮችን የገቢ አሰባሰብን በቴክኖሎጂ በመደገፍ ወጪ ቆጣቢ ቀልጣፋ አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ የአስተዳደሩ ገቢን ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል።
የተሻሻለው የፌደራል ገቢ ግብር አዋጅ ቁጥር 1395/2017 የታክስ ማጭበርበርን
በመከላከል እንዲሁም ዝቅተኛ ገቢ ያለው የህብረተሰብ ክፍል የሚያርፍበትን የግብር ጫና በመቀነስ የህዝቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በመረጋገጥ በኩል ጉልህ ሚና እንዳለው አስረድተዋል።


