በድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ የአእምሮ ጤና ላይ ያተኮረ ወርክ ሾፕ ተካሄደ::

የድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ ከአሊ ቢራ ፋውንዴሽን እንዲሁም ከአሜሪካ ሚኒሶታ ዩኒቨርስቲ ጋር በመተባበር የስነ አእምሮ ጤና ላይ ያተኮረ ወርክ ሾፕ በዛሬው ዕለተ አካሄደ::

በመድረኩ የተገኙት የድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ የህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ኃላፊ አቶ ሁሴን መሀመድ የዚህ ወርክ ሾፕ ዋንኛ አላማ ለማህበረሰቡ የስነ አእምሮ ጤና ላይ ግንዘቤ መፍጠር ነው ሲሉ አብራርተዋል:: በተለይም የበሽታውን የስርጭት መጠን ለመቀነስ ቅድመ ጥንቃቄ ላይ ተተኩሮ መሰራት እንደሚገባውም አቶ ሁሴን አመላክተዋል::

ከአሜሪካ ሚኒሶታ ዩኒቨርስቲ ተጋብዘው የመጡት ፕሮፌሰር ሙስጠፋ አል አብሲን በመድረኩ በጫት ዙሪያ ጥናታዊ ፅሁፍ ያቀረቡ ሲሆን በአእምሮ ጤና አጠባበቅ ላይ በየጊዜው የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮችን መፈጠር እንደሚገባ ተናግረዋል::

ፕሮፌሰሩ አያይዘውም በቀጣይ የአሜሪካ ሚኒሶታ ዩኒቨርስቲ ከድሬዳዋ ዩኒቨርስቲና ከአሊ ቢራ ፋውንዴሽን ጋር የሚሰራቸውን በጎ ስራዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቁመዋል::

በወርክ ሾፑ በአደንዛዥ እፅ ዙሪያ እንዲሁም የኢትዮጲያ የአእምሮ ጤናን በተመለከተና የህፃናትና የወጣቶች የአይምሮ ጤና ላይ ጥናታዊ ፅሁፎች ቀርበው ከመድረኩ ሃሳብ አስተያየት ተሰቶበት ውይይት ተደርጓል::

በተያያዘ ዜናም በወርክ ሾፑ ማጠቃለያ የድሬዳዋ ዩኒቨርስቲ መማሪያና ሪፈራል ሆስፒታል የስነ አእምሮ ጤና ክፍል በድምቀት ተመርቋል::

ይህ የህክምና ማዕከልም ወደስራ መግባቱ በመስተዳደሩን የስነ አእምሮ ጤና ህክምና ደረጃ ከፍ እንደሚያደርገው ተገልፇል::

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *