በቀጣይ ቀናትም የጎርፍ አደጋ ሊደርስ ስለሚችል ህብረተሰቡ ተገቢውን ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ ተጠቆመ::

    በድሬደዋ ከተማ በትናንትናው ዕለት በጣለው ከባድ ዝናብ ሳቢያ የአንድ መኖሪያ ቤት አጥር ግንብ ፈርሶ በመኖሪያ ቤት ላይ በመውደቁ የሶስት ሰዎች ህይወት ያለፈ ሲሆን በመብረቅ አደጋም የአንድ ሰው ህይወት ማለፉ ታውቋል፡፡
    በድሬዳዋ ከተማ ቀበሌ 08 ልዩ ስሙ ለገሃሬ ከመንገድ በላይ ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ ከለሊቱ ዘጠኝ ሰአት ጀምሮ በጣለው ከባድ ዝናብ የአንድ መኖሪያ ቤት አጥር ተደርምሶ በአቅራቢያው ባለው መኖሪያ ቤት ላይ በመውደቁ የሶስት ሰዎች ህይወት ማለፉን እና ቀላልና ከባድ የአካል ጉዳት መድረሱን የአስተዳደሩ ፖሊስ ኮሚሽን የህዝብ ግንኙነት እና ለውጥ ስራ አመራር ዳሬክቶሬት ዳሬክተር ኮማንደር ገመቹ ካቻ ገልጸዋል፡፡
    ከሞቱት ሰዎች መካከልም የ12 አመት ፤የሶስት አመት እና የሁለት ወር ህጻን ልጅ በአደጋው ህይወታቸው ሲያልፍ፤ የልጆቹ ወላጅ እናት እና አንድ ወንድ ልጃቸው ላይ ከባድ የአካል ጉዳት ደርሶባቸው በድልጮራ ሪፈራል ሆስፒታል በህክምና ላይ እንደሚገኙ ኮማንደሩ አክለው ተናግረዋል፡፡ በልጆቹ አባት ላይ ቀላል የአካል ጉዳት መድረሱን ኮማንደር ገመቹ ካቻ ጠቁመዋል::
    በተያያዘም በድሬዳዋ ከተማ ቀበሌ 01 መልካ ጀብዱ ከቀኑ ዘጠኝ ሰአት በኢትዮ-ጅቡቲ ምድር ባቡር ግቢ ውስጥ በስራ ላይ በነበሩ ሁለት ግለሰቦች ላይ መብረቅ በመውደቁ፤ በአንደኛው ግለሰብ ላይ የሞት አደጋ ሲያስከትል በሌላው ግለሰብ ላይ የአካል ጉዳት ደርሶበታል፡፡ ግለሰቡም በማርያም ወርቅ ሆስፒታል በህክምና ላይ እንደሚገኙ ኮማንደሩ አያይዘው ተናግረዋል፡፡
    ባሳለፍነው ሚያዝያ 24 ቀን 2013 ዓ.ም በድሬዳዋ ከተማ በጣለው ከባድ ዝናብ የአንድ ድርጅት ቅጥር ፈርሶ በአደጋው የዘጠኝ ሰዎች ህይወት ማለፉን ኮማንደሩ ጠቁመዋል፡፡ በቀጣይ ቀናትም ዝናብ ጥሎ የጎርፍ አደጋ ሊደርስ ስለሚችል ህብረተሰቡ ተገቢውን ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ ኮማንደር ገመቹ አክለውም የአስተዳደሩ ፖሊስ ኮሚሽን በድንገት ሊከሰት ከሚችለው የጎርፍ አደጋ ጋር ተያይዞ ህብረተሰቡ ቅድመ-ጥንቃቄ እንዲያደርግ ከተለያዩ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
    ኮማነደሩ የድሬደዋ አስተዳደር ፖሊስ ኮሚሽን በአደጋው በደረሰው ህልፈተ-ህይወት የተሰማውን ልባዊ ሀዘን ገለጿል ብለዋል፡፡