ወጣቶች ሀገርን በማስከበር ያከናወኑትን አኩሪ ተግባር በልማት እየደገሙት መሆኑ ተገለጸ

    ወጣቶች የሀገር ሉዓላዊነትን ለማስከበር እያከናወኑት ያለውን አኩሪ ተግባር በዘላቂ ልማቱ ላይ ለመድገም እየተረባረቡ መሆናቸውን የሴቶች እና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ፡፡
    የሴቶች እና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ኤርጎጌ ተስፋዬ ዛሬ በድሬዳዋ ከተማ ሀገር አቀፍ የወጣቶች የበጎ ፈቃድ አገልግሎትን አስጀምረዋል፡፡
    ሚኒስትሯ በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር÷ ወጣቶች ባለፉት ዓመታት ባከናወኗቸው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተግባራት በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቁመው÷ በዚህም በቢሊየን የሚገመት ገንዘብ ከወጪ በማዳን በሀገሪቱ ምጣኔ ሃብታዊና ማህበራዊ አገልግሎት ላይ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን አስታውሰዋል።
    በመላው ሀገሪቱ በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ላይ እየተሳተፉ የሚገኙ ወጣቶች የሀገርን ዳር ድንበር ለማስከበር ያከናወኑትን አኩሪ ተግባራት በልማቱ ላይ እየደገሙት ነው ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡